ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ኢትዮጵያ ታምርት' ኤክስፖ 2018 በይፋ መርቀው ከፈቱ
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የኢትዮጵያን የአምራች ዘርፍ ለማስፋፋት የሚደረገውን ጥረት የሚያጠናክረውን አራተኛውን 'ኢትዮጵያ ታምርት' ኤክስፖ 2018 ዛሬ በይፋ መርቀው ከፍተዋል።
ኤክስፖው እስካሁን ያሳያቸው እና የተመዘገቡ ዋና ዋና ስኬቶች፦
- የአምራች ዘርፉ ግብዓት አቅርቦት በዓመት ከ9 ሚሊዮን ወደ 15 ሚሊዮን ቶን አድጓል፤
- ለአዳዲስ የኢንዱስትሪ ኢንቨስትመንቶች ከ3.4 ጊጋ ዋት በላይ የኤሌክትሪክ ኃይል ቀርቧል፤
- ለአነስተኛ እና መካከለኛ ኢንተርፕራይዞች የሚቀርበው የፋይናንስ አቅርቦት ከ8.1 ቢሊዮን ወደ 50 ቢሊዮን ብር ያደገ ሲሆን፣ ለከፍተኛ ኢንዱስትሪዎች ደግሞ ከ262 ቢሊዮን ብር በላይ ከፍ ብሏል፤
- ለዘርፉ ከ2.28 ቢሊዮን ዶላር በላይ የውጭ ምንዛሬ ተመድቧል፤
- የፋብሪካዎች የማምረት አቅም ከ47 በመቶ ወደ 67 በመቶ አድጓል፤
- የማምረት አቅም እና ዕድገት ከ4.8 በመቶ ወደ 10.7 በመቶ ከፍ ያለ ሲሆን፣ በቀጣይም ተጨማሪ ዕድገት ይጠበቃል፤
- ምርትን በሀገር ውስጥ በመተካት እስከ 4.85 ቢሊዮን ዶላር ማዳን የተቻለ ሲሆን የወጪ ንግድም ከፍተኛ እድገት እያሳየ ይገኛል፤
- ከ2 ሺህ 800 በላይ ኢንቨስትመንቶችን መሳብ የተቻለ ሲሆን፣ ለ1.4 ሚሊዮን ዜጎች የሥራ ዕድል ተፈጥሯል።
ኤክስፖው ኢንዱስትሪዎችን የሚያስተሳስር፣ ኢንቨስትመንትን የሚስብ፣ በመቶዎች የሚቆጠሩ አምራቾችን እና በአሥር ሺዎች የሚቆጠሩ ጎብኚዎችን የሚያገናኝ ቁልፍ ሀገራዊ መድረክ ሆኗል።
በአጠቃላይ የኤክስፖው መከፈት የአምራች ዘርፉ ለኢኮኖሚ ዕድገት፣ ለሥራ ዕድል ፈጠራና ለዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነት ያለውን ፋይዳ በማጉላት የኢትዮጵያን የኢንዱስትሪ ሽግግር እያፋጠነ መሆኑን ያሳያል።