ኢትዮጵያ እና ኬንያ የኢንዱስትሪ እና ኢንቨስትመንት ትስስራቸውን በሚያጠናክሩ ጉዳዮች ዙሪያ ተወያዩ

የካቲት 27/2018 ዓ.ም (ኢሚ)የኢንዱስትሪ ሚኒስትር አቶ ታረቀኝ ቡሉልታ በኬኒያ ኢንዱስትሪ ዘርፍ ዋና ጸሃፊ ዶ/ር ጁማ ሙካሀዋና የተመራ ልዑክ በቢሮዋቸው ተቀብለው አናግረዋል፡፡

የውይይታቸው ዋና ትኩረት በሁለቱ አገራት የንግድ፣ ኢንዱስትሪና ኢንቨስትመንት ትስስር በተለይም በቆዳ ኢንዱስትሪ ዘርፍ ያለውን ትስስር ማጠናከር እና የመልካም ተሞክሮ ቅመራ ላይ ያተኮረ ነው፡፡

ኢትዮጵያና ኬንያ በመከባበር፣ በመተባበር እና በኢኮኖሚ እድገትና በቀጣናዊ ውህደት ላይ የተመሰረተ ረጅም ዘመን ያስቆጠረ አጋርነት እንዳላቸው የገለጹት የአንዱስትሪ ሚኒስትር ዴኤታ አቶ ታረቀኝ ቡሉልታ ለአምራች ኢንዱሰትሪ እድገት፣ ቅንጅትን ለማጠናከር እና ቀጣይነት ያለው የኢኮኖሚ እድገት እና ለውጥ ለማምጣት በጋራ መስራት ወሳኝነት እንዳለው ገልጸዋል፡፡

እንደ ሀገር መንግስት ልዩ ትኩረት ከተሰጣቸው ዋና ዋና ዘርፎች መካከል አምራች ኢንዱስትሪ አንዱ እንደሆነ የገለጹት አቶ ታረቀኝ በዚህም ዘርፉን ወደ ተሻለ ምዕራፍ ለማሸገርና በሀገራዊ እድገት ላይ ያለውን ድርሻ ለማሳደግ ከፖሊሲ ዝግጅት ጀምሮ አስፈላጊ የህግ ማዕቀፎች መዘጋጀታቸውን፣ የአምራች ኢንዱስትሪ ፖሊሲ ዓላማ ፣ዋና ዋና የትኩረት አቅጣጫዎች እና የተገኙ ውጤቶችን አብራርተዋል፡፡

በዘርፉ የተወሰዱ እርምጃዎችን ተከትሎም ከውጪ ወደ ሀገር ውስጥ የሚገቡ ምርቶችን በሀገር ውስጥ ምርት በመተካት፣ የወጪ ምርት እድገት፣ የሀገር ውስጥ የገበያ ድርሻ፣ የማምረት አቅም አጠቃቀም፣ በተቋማት ቅንጅት ዙሪያ መልካም ውጤቶች መመዝገባቸውን አቶ ታረቀኝ ገልጸዋል፡፡

የኬንያው ኢንዱስትሪ ዘርፍ ዋና ጸሃፊ ዶ/ር ጁማ ሙካሀዋና በበኩላቸው አፍሪካ ትልቅ የህዝብ ብዛት ያላት ቢሆንም በአምራች ኢንዱስትሪ ያላት የገበያ ድርሻ ከ 3 በመቶ በላይ የማይዘል መሆኑን ገልጸው እንዚህንና መሰል ችግሮች ለመቅረፍ አፍሪካውያን የንግድ ኢንዱስትሪና ኢንቨስትመንት ትስስራቸውን ማጠናከር ይገባቸዋል ሲሉ ገልጸዋል፡፡

እንደ ሀገር ያላቸውን ጥንካሬ ያነሱት ዋና ጸሃፊው የኢትዮጵያ ባለሃብቶች በግብርና፣ በቆዳና ቆዳ ውጤቶች ፣ በፋርማሲዩቲካል፣በመንገድ ግንባታ ፣በሲሚንቶ በፋይናስ እና ሌሎች ዘርፎች እንዲሰማሩ ጥሪያቸውን አቅርበዋል፡፡

በውይይቱ በሁለቱም ሀገራት በአምራች ኢንዱስትሪ ዘርፍ ስላሉ መልካም አጋጣሚዎች እና እያጋጠሙ ባሉ ትግዳሮቶች እንዲሁም የመፍትሄ አቅጣጫዎች ዙሪያ ውይይት ተካሂዷል፡፡

Share this Post